group-telegram.com/ETH724/2
Last Update:
ዓርብ ነሐሴ 7/2013 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች
1፤ ፈረንሳይ የኢትዮጵያን ባሕር ኃይል መልሶ ለማደራጀት የገባችውን ወታደራዊ ስምምነት
እንደሰረዘች የፈረንሳዩ ዜና ወኪል የፈረንሳይ ባለሥልጣናትን በምንጭነት ጠቅሶ ዘግቧል።
ፈረንሳይ ወታደራዊ ትብብሯን ባለፈው ወር ያቋረጠችው በሰሜን ኢትዮጵያ ካለው ጦርነት
ጋር በተያያዘ እንደሆነ መሆኑን ዘገባው ገልጧል። ፈረንሳይ ያቋረጠችው የትብብር
ስምምነት፣ የኢትዮጵያ ባሕር ኃይልን ለማደራጀት እና ለማዘመን የ100 ሚሊዮን ዶላር ብድር
ለመስጠት ከሁለት ዓመት ከመንፈቅ በፊት በፕሬዚዳንት ማክሮን እና በጠቅላይ ሚንስትር
ዐቢይ መካከል የተደረሰውን ስምምነት ነው።
2፤ በአፍሪካ ቀንድ የአሜሪካ ልዩ መልዕክተኛ ጀፍሪ ፊልትማን በድጋሚ ወደ ኢትዮጵያ ሊሄዱ
እንደሆነ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚንስቴር ባሰራጨው መረጃ አስታውቋል። ፊልትማን
ከዕሁድ ጀምሮ በኢትዮጵያ፣ ጅቡቲ እና የተባበሩት ዐረብ ኢምሬቶች ለ10 ቀናት በሚያደርጉት
ጉብኝት፣ አሜሪካ ለአፍሪካ ቀንድ ሰላምና መረጋጋት ልታደርገው በምትችለው አስተዋጽዖ
ዙሪያ ከየሀገራቱ ባለሥልጣናት ጋር እንደሚነጋገሩ መግለጫው ጠቁሟል። ፊልትማን
በተለይ ለሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት መፍትሄ ለማፈላለግ በድጋሚ ወደ ኢትዮጵያ እንዲሄዱ
ያዘዟቸው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን እንደሆኑ የፕሬዝዳንቱ ብሄራዊ ደኅንነት አማካሪ ጄክ ሱሊቫን
በትዊተር ገጻቸው ገልጠዋል።
3፤ የሕወሃት ተዋጊዎች የተቆጣጠሯቸውን የአማራ እና አፋር ክልል ቦታዎች እንደማይለቁ
የሕወሃት ቃል አቀባይ ጌታቸው ረዳ ዛሬ ከቢቢሲ ሐርድ ቶክ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ
ተናግረዋል። የሕወሃት ኃይሎች ለተኩስ አቁም ዝግጁ የሚሆኑት፣ ቢያንስ መንግሥት
ለትግራይ ክልል ያቋረጣቸውን መሠረተ ልማቶች እንደገና ሲያስጀምር እንደሆነ ጌታቸው
ጠቁመዋል። ትግራይን መገንጠል ቀዳሚ የሕወሃት አጀንዳ እንዳልሆነ የገለጡት ጌታቸው፣
የትግራይን ሕዝብ የራሱን ዕድል በራሱ የመወሰን መብቱ ግን እንዲተገበር እናደርጋለን
ብለዋል። ከሳምንት በፊት በአፋር ክልል በበርካታ ተፈናቃዮች ላይ የሕወሃት ተዋጊዎች
ስለፈጸሙት ግድያ ጌታቸው ተጠይቀው፣ ክስተቱ በገለልተኛ አካል እንዲጣራ ጠይቀዋል።
ሕወሃት ከአማጺው የኦሮሞ ነጻ አውጭ ሠራዊት ጋር ወታደራዊ ትብብር መመስረቱንም
ጌታቸው በቃለ ምልልሳቸው አረጋግጠዋል።
4፤ የሕወሃት ተዋጊዎች በአማራ ክልል ከሰሜን ወሎዋ ወልድያ ከተማ ወደ ደቡብ ጎንደሯ
ወረታ ከተማ በሚወስደው መስመር ላይ ሰሞኑን ባካሄዱት ወታደራዊ ዘመቻ አንዳንድ
ከተሞችን እንደተቆጣጠሩ የትግራይ ክልል ቴሌቪዥን ዘግቧል። የሕወሃት ተዋጊዎች ከአማራ
ክልል ታጣቂዎች አስለቅቀናል ያሉት የታች ጋይንት ወረዳ ዋና ከተማ የሆነችውን ንፋስ
መውጫን፣ የሰሜን ወሎዋን ደብረ ዘቢጥን እና ጨጨሆ የተባሉ ሌሎች ከተሞችን ነው።
ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ሰዓት ድረስ የተጠቀሱት ከተሞች በሕወሃት ተዋጊዎች
ስለመያዛቸው የአማራ ክልል መንግሥት ማረጋገጫም ይሁን ማስተባበያ አልሰጠም።
5፤ አፍሪካ ኅብረት ስለ ትግራዩ ጦርነት ዛሬ በኦፊሴላዊ ትዊተር ገጹ ላይ ተለጥፎ የነበረው
መልዕክት የኅብረቱን አቋም የማይወክል በመሆኑ ባስቸኳይ ማንሳቱን ኅብረቱ በትዊተር ገጹ
አስታውቋል። በኅብረቱ ኦፊሴላዊ ትዊተር ገጽ ላይ የወጣው መልዕክት፣ አሜሪካ
ከአፍጋኒስታኑ ታሊባን ጋር እንደተደራደረችው የኢትዮጵያ መንግሥትም ከአሸባሪው ሕወሃት
ጋር ይደራደር ማለት ከሆነ ያ ፈጽሞ አይደረግም የሚል ይዘት ያለው ነበር። የኅብረቱን
የሠራተኛ ስነ ምግባር ደንብ በጣሰ መልኩ የግል አስተያየቱን በኅብረቱ ትዊተር ገጽ ላይ
የጻፈው አንድ የኅብረቱ ባልደረባ ያለው ድርጅቱ፣ ጉዳዩን እያጣራ መሆኑን ገልጧል።
6፤ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት በትግራይ ክልል ከሚገኙት መቀሌ፣ አዲግራት፣ አክሱም፣ እና
ራያ ዩኒቨርስቲዎች ከ10 ሺህ 100 በላይ ተማሪዎችን ወደ ቀያቸው መመለሱን የሳይንስና
ከፍተኛ ትምህርት ሚንስቴር ዛሬ በድረገጹ
ባሰራጨው መግለጫ አስታውቋል። ከአክሱም እና አዲግራት ዩኒቨርስቲዎች ዘንድሮ
ለመመረቅ አንዳንድ ትምህርቶች የቀሯቸው ተማሪዎች ወደፊት ትምህርቶቹን
የሚያጠናቅቁበትን መርሃ ግብር በሂደት አሳውቃለሁ- ብሏል ሚንስቴሩ። የሁሉም ተቋማት
ተማሪዎች የክረምት ዕረፍት በጸጥታ ችግር ሳቢያ ላንድ ወር በመዘግየቱ የዕረፍት ጊዜው
እንደሚያራዝም ሚንስቴሩ አክሎ ገልጧል።
7፤ ከአዲስ አበባ ወደ ባሕርዳር የሚወስደው ዋናው የእስፓልት መንገድ ዓባይ በረሃ ላይ
የመሬት መንሸራተት በመከሰቱ የየብስ መጓጓዣ እንደተቋረጠ የኢትዮጵያ መንገዶች
ባለሥልጣን በማኅበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል። ትናንት ሌሊት የድንጋይ ናዳ መንገዱ ላይ
የተከሰተው ልዩ ስሙ ፍልቅልቅ የተባለ ቦታ ላይ መሆኑን የገለጠው ባለሥልጣኑ፣ መንገዱን
በአስቸኳይ የሚጠግን ግብረ ኃይል ወደ ሥፍራው ተንቀሳቅሷል ብሏል።
8፤ ዓለማቀፉ ድንበር የለሽ የሐኪሞች ቡድን ከወራት በፊት በትግራይ ክልል በሦስት
ሠራተኞቹ ላይ የተፈጸመው ግድያ እንዲጣራለት በትዊተር ገጹ ባሰፈረው ጥሪ በድጋሚ
ጠይቋል። እስካሁን የሦስቱ ባልደረቦቹን ገዳዮች ማንነት እንደማያውቅ የገለጠው ቡድኑ፣
በወቅቱ በትግራይ ክልል የነበሩ ሁሉም የግጭቱ አካላት ግድያውን ለማጣራት እንዲተባበሩ
ጥሪ አድርጓል። ሰላም ሚንስቴር ግድያውን እና የገዳዮቹን ማንነት ለማጣራት እያደረገው
ያለውን ምርመራ እንደሚያደንቅ ቡድኑ አክሎ ገልጧል።
@ETH724
@ETH724
BY ኢትዮ 7/24 መረጃ
Warning: Undefined variable $i in /var/www/group-telegram/post.php on line 260
Share with your friend now:
group-telegram.com/ETH724/2